am_obs/content/16.md

75 lines
9.9 KiB
Markdown

# 16. ነፃ አውጪዎቹ
![OBS Image](https://cdn.door43.org/obs/jpg/360px/obs-en-16-01.jpg)
ኢያሱ ከሞተ በኋላ፣ እስራኤላውያን እግዚአብሔርን አልታዘዙም፤ የቀሩትንም ከነዓናውያን ከመካከላቸው አላስወጡም ወይም የእግዚአብሔርን ሕግ አልታዘዙም። እስራኤላውያን እውነተኛ አምላክ የሆነውን ያህዌን ከማምለክ ይልቅ የከነዓናውያንን አማልክት ማምለክ ጀመሩ። እስራኤላውያን ንጉሥ አልነበራቸውም፣ ስለዚህ እያንዳንዱ ትክክል መስሎ የሚታየውን ሁሉ ያደርግ ነበር።
![OBS Image](https://cdn.door43.org/obs/jpg/360px/obs-en-16-02.jpg)
እስራኤላውያን እግዚአብሔርን አለመታዘዛቸውን በመቀጠላቸው፣ እግዚአብሔር ጠላቶቻቸውን እንዲያጠቁአቸው አደረገ። እነዚህ ጠላቶቻቸው የእስራኤላውያንን እቃዎች ሁሉ ሰረቁ፣ ንብረታቸውንም አወደሙ፣ አብዛኞቻቸውንም ገደሉ። እስራኤላውያን እግዚአብሔርን ባለመታዘዝና በጠላቶቻቸው በመጨቆን ብዙ ዘመናትን ካሳለፉ በኋላ፣ ንስሐ ገቡ እግዚአብሔርንም ከጠላቶቻቸው እንዲያድናቸው ጠየቁ።
![OBS Image](https://cdn.door43.org/obs/jpg/360px/obs-en-16-03.jpg)
ከዚያም እግዚአብሔር ከጠላቶቻቸው የሚያድናቸው ነፃ አውጪ ላከላቸው ለምድሪቱም ሰላምን አመጣ። ነገር ግን ሰዎቹ እግዚአብሔርን እንደ ገና ረሱ። ጣዖትንም ማምለክ ጀመሩ፤ ስለ ሆነም እግዚአብሔር በአቅራቢያቸው የሚገኙትን ጠላቶቻቸውን ምድያማውያንን አስንሣባቸው፣ አሸነፉአቸውም።
![OBS Image](https://cdn.door43.org/obs/jpg/360px/obs-en-16-04.jpg)
ምድያማውያን የእስራኤላውያንን ሰብል ሁሉ ለሰባት ዓመታት ወሰዱ። እስራኤላውያን በጣም ፈርተው ነበር፣ በየሸለቆውና በየዋሻው ተሸሽገው ስለ ነበር ምድያማውያን ሊያገኙአቸው አልቻሉም። በመጨረሻም እንዲያድናቸው ወደ እግዚአብሔር ጮኹ።
![OBS Image](https://cdn.door43.org/obs/jpg/360px/obs-en-16-05.jpg)
አንድ ቀን፣ ጌዴዎን የሚባል እስራኤላዊ ምድያማውያን ሰብሉን እንዳይወስዱበት ተደብቆ እህል ይወቃ ነበር። የእግዚአብሔርም መልአክ ወደ ጌዴዎን መጥቶ እንዲህ አለው “አንተ ብርቱ ተዋጊ ሰው እግዚአብሔር ከአንተ ጋር ነው። ሂድና እስራኤልን ከምድያማውያን አድን።”
![OBS Image](https://cdn.door43.org/obs/jpg/360px/obs-en-16-06.jpg)
የጌዴዎን አባት ለጣዖት አምልኮ የተዘጋጀ መሠዊያ ነበረው። እግዚአብሔርም ጌዴዎንን ያንን መሠዊያ እንዲያፈርስ ተናገረው። ነገር ግን ጌዴዎን ሕዝቡን ስለ ፈራ እስኪመሽ ድረስ ጠበቀ። ከዚያም መሠዊያውን አፈራረሰው እስኪደቅቅ ድረስም ሰባበረው። በአጠገቡም ለእግዚአብሔር ዐዲስ መሠዊያን አዘጋጀ። ለእግዚአብሔር መሥዋዕትን ሠዋበት።
![OBS Image](https://cdn.door43.org/obs/jpg/360px/obs-en-16-07.jpg)
በማግስቱ ጠዋት ሕዝቡ አንድ ሰው መሠዊያቸውን እንዳፈራረሰው ተመልክተው እጅግ ተበሳጩ። ጌዴዎንን ለመግደል ወደ ጌዴዎን ቤት ሄዱ። ነገር ግን የጌዴዎን አባት “ለምን አምላካችሁን ለማገዝ ትሞክራላችሁ? እርሱ አምላክ ከሆነ ራሱን ይከላከል!” አላቸው። ይህንንም ስላለ ሕዝቡ ጌዴዎንን አልገደሉትም።
![OBS Image](https://cdn.door43.org/obs/jpg/360px/obs-en-16-08.jpg)
ምድያማውያን አስራኤላውያንን ለመዝረፍ እንደ ገና መጡ። ቊጥራቸው እጅግ ብዙ ስለ ነበር ማንም ሊቈጥራቸው አይችልም ነበር። ጌዴዎንም ምድያማውያንን ለመውጋት እስራኤላውያንን ጠራ። እግዚአብሔር እርሱን ተጠቅሞ እስራኤልን ያድን እንደ ሆነ ለማረጋገጥ ጌዴዎን ሁለት ምልክቶችን ከእግዚአብሔር ጠየቀ።
![OBS Image](https://cdn.door43.org/obs/jpg/360px/obs-en-16-09.jpg)
ለመጀመሪያው ምልክት ጨርቅ በምድር ላይ አድርጎ የጠዋቱ ጤዛ በጨርቁ ላይ ብቻ እንጂ በምድር ላይ እንዳይሆን ጠየቀ። እግዚአብሔርም እንደዚያው አደረገ። በሚቀጥለው ምሽት ጌዴዎን እግዚአብሔርን እንዲህ ብሎ ጠየቀ፤ መሬቱ በጠዋቱ ጤዛ እንዲረጥብ ጨርቁ ግን ደረቅ ይሁን አለ። እግዚአብሔርም እንደዚያው አደረገ። እነዚህ ሁለቱ ምልክቶች እግዚአብሔር እርሱን ተጠቅሞ እስራኤልን ከምድያም እንደሚያድን ለጌዴዎን ማስረጃ ሆኑለት።
![OBS Image](https://cdn.door43.org/obs/jpg/360px/obs-en-16-10.jpg)
32,000 እስራኤላውያን ወታደሮች ወደ ጌዴዎን መጡ፣ ነገር ግን እግዚአብሔር ቊጥራቸው ብዙ ነው አለው። ስለዚህ ጌዴዎን መዋጋት የፈሩትን 22,000 ወታደሮችን ወደ ቤታቸው መለሳቸው። እግዚአብሔር ጌዴዎንን አሁንም የወታደሩ ቊጥር ብዙ ነው አለው። ስለሆነም ጌዴዎን 300 ወታደሮችን አስቀርቶ ሌሎቹን ወደ ቤታቸው መለሳቸው።
![OBS Image](https://cdn.door43.org/obs/jpg/360px/obs-en-16-11.jpg)
በዚያን ሌሊት እግዚአብሔር ጌዴዎንን “ወደ ምድያማውያን ጦር ሠፈር ውረድ፣ የሚሉትንም ብትሰማ ፈጽመህ አትፍራቸው” አለው። ስለ ሆነም ጌዴዎን ወደ ምድያማውያን ጦር ሠፈር በዚያው ሌሊት ወረደ አንድ የምድያም ወታደር ለጓደኛው በሕልሙ “የጌዴዎን ጦር የምድያምን ጦር ሲያሸንፍ” እንዳየ ሲነገረው ሰማ። ጌዴዎን ይህን በሰማ ጊዜ ለእግዚአብሔር ሰገደ።
![OBS Image](https://cdn.door43.org/obs/jpg/360px/obs-en-16-12.jpg)
ከዚያም ጌዴዎን ወደ ወታደሮቹ ተመልሶ ለእያንዳንዳቸው ቀንደ መለከት፣ ማሰሮ እና ችቦ ሰጣቸው። የምድያም ሠራዊት ተኝቶ እያለ ሰፍሮ የነበረበትን የጦር ሠፈር ከበቡ። የጌድዎን 300 ወታደሮች በማሰሮው ውስጥ ችቦ ይዘው ነበር፣ የምድያም ወታደሮች ግን የችቦውን ብርሃን ማየት አልቻሉም።
![OBS Image](https://cdn.door43.org/obs/jpg/360px/obs-en-16-13.jpg)
ከዚያም የጌዴዎን ወታሮች በሙሉ በተመሳሳይ ጊዜ ማሰሮዎቻቸውን ሰበሩ ወዲያው የችቦው ብርሃን በድንገት አበራ። ቀንደ መለከታቸውን እየነፉ “የእግዚአብሔርና የጌዴዎን ሠራዊት” እያሉ ጮኹ።
![OBS Image](https://cdn.door43.org/obs/jpg/360px/obs-en-16-14.jpg)
እግዚአብሔርም ምድያማውያንን ግራ አጋባቸው፣ እርስ በርሳቸውም ተገዳደሉ። ወዲያው በየቤታቸው ያሉ እስራኤላውያን ተጠርተው ምድያማውያንን ለማባረር ተረዳዱ። ብዙዎችን ገደሉ የተቀሩቱንም ከእስራኤል ምድር አባረሩ። በዚያን ጊዜ 120,000 የምድያም ወታደሮች ሞቱ። እግዚአብሔርም እስራኤልን አዳነ።
![OBS Image](https://cdn.door43.org/obs/jpg/360px/obs-en-16-15.jpg)
ሕዝቡም ጌዴዎንን ንጉሣቸው እንዲሆን ፈለጉ። ጌዴዎን ግን ይህን እንዲያደርጉ አልፈቀደላቸውም፤ ነገር ግን እያንዳንዳቸው ከምድያማውያን የወሰዱአቸውን የወርቅ ቀለበት እንዲያመጡ ጠየቃቸው። ሕዝቡም ለጌዴዎን እጅግ ብዙ ወርቅ ሰጡት።
![OBS Image](https://cdn.door43.org/obs/jpg/360px/obs-en-16-16.jpg)
ጌዴዎንም ወርቁን አቅልጦ ሊቀ ካህኑ እንደሚለብሰው ልዩ ልብስ አድርጎ አሠራው። ነገር ግን ሕዝቡ ያንን ልብስ እንደ ጣዖት ሊያመልኩት ጀመሩ። ከዚያም የተነሣ እግዚአብሔር ጠላቶቻቸው እንዲያሸንፉአቸው አድርጎ ቀጣቸው። በመጨረሻም ሕዝቡ አሁንም እግዚአብሔር እንዲያድናቸው ጠየቁ፣ እግዚአብሔር ሌላ አዳኝ ላከላቸው።
![OBS Image](https://cdn.door43.org/obs/jpg/360px/obs-en-16-17.jpg)
እንዲህ ያለው ሁኔታ ብዙ ጊዜ ተደጋገመ። እስራኤላውያን ኃጢአትን ያደርጋሉ፣ እግዚአብሔር ይቀጣቸዋል፣ እንደ ገና ንስሐ ይገባሉ፣ እግዚአብሔርም ያድናቸው ዘንድ አዳኝን ይልክላቸዋል። ለብዙ ዓመታት እግዚአብሔር እስራኤልን ለማዳን ብዙ ነፃ አውጪዎችን ልኮላቸዋል።
![OBS Image](https://cdn.door43.org/obs/jpg/360px/obs-en-16-18.jpg)
በመጨረሻም፣ ሕዝቡ ሌሎቹ አሕዛብ እንዳሉአቸው ንጉሥን እንዲሰጣቸው እግዚአብሔርን ጠየቁ። በጦርነት የሚመራቸው፣ ረጅምና ጠንካራ የሆነ ንጉሥ እንዲኖራቸው ፈለጉ። እግዚአብሔር ግን ይህንን ጥያቄአቸውን አልወደደም፣ ሆኖም እንደ ፈለጉት ንጉሥን ሰጣቸው።
_የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- መሳፍንት 1-5፣ 6-8።_